የአማራ ክልል ምክር ቤት የተቋማትን ፋይናንስ ሲከታተል እና ሲቆጣጠር የሚያጋጥሙትን ችግሮች ለመፍታት የሚያስችል ሥልጠና መሰጠቱ ተገለጸ።
ባሕር ዳር: ኅዳር 23/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የክልሉ ገንዘብ ቢሮ በመንግሥት ግዥ እና ፋይናንስ አሥተዳደር ዙሪያ ለክልል ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ ሠብሣቢዎች እና አባላት ሥልጠና እየሰጠ ነው። በአማራ ክልል ምክር ቤት የመንግሥት ወጭ አሥተዳደር ቋሚ ኮሚቴ አባል እናትነሽ በዛብህ እንዳሉት የመንግሥት ወጭን በተገቢው መንገድ ለማሥተዳደር ሥልጠናው የግንዛቤ ክፍተትን የሚሞላ ነው። እያንዳንዱ የበጀት ተጠቃሚ የመንግሥት መስሪያ ቤት የሚያወጣውን ወጭ ተከታትሎ ለመደገፍ አቅምን የሚያጎለብት ሥልጠና እንደኾነ ነው የተገለጸው። ችግሮችም ካሉ በዕውቀት ላይ ተመስርቶ ለማረም ሥልጠናው ዓይነተኛ ሚና ይጫወታል። በአማራ ክልል ምክር ቤት የበጀት እና ፋይናንስ ቋሚ ኮሚቴ ሠብሣቢ ሃናን አብዱ በገንዘብ ቢሮ ባለሙያዎች እየተሰጠ ያለውን ሥልጠና እየወሰዱ የሚገኙት በክልሉ በበጀት የሚተዳደሩ የመንግሥት ተቋማትን የሚቆጣጠሩ እንደመኾናቸው ሥልጠናው በቂ ዕውቀት ለመጨበጥ ያስችላቸዋል ብለዋል። አላስፈላጊ የበጀት ብክነት እንዳይኖር እንደሚረዳቸውም ነው ያስገነዘቡት። ሥልጠናው ሰፊ ፋይዳ አለው ያሉት ሠብሣቢዋ የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ የሚመነጨው ከበጀት ጋር ተያይዞ ነው፤ ስለኾነም ብልሹ አሠራርን ለማስተካከል ሥልጠናው እርሾው ከፍተኛ ነው ብለዋል። በአማራ ክልል ምክር ቤት የክትትል እና አሥተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሠብሣቢ ደሴ ጥላሁን (ዶ.ር) በክልሉ በጀት እና ፋይናንስ አሥተዳደር ዙሪያ እየተሰጠ ያለው ሥልጠና የክልሉ ምክር ቤት በየጊዜው የሚያጸድቀው በጀት በአግባቡ መተዳደሩን፣ በሕግ አግባብ እየተመራ ስለመኾኑ እና ለታለመለት ዓላማ ሥራ ላይ ስለመዋሉ እየተከታተለ የቁጥጥር ሥራ ስለሚያከናውን ሥልጠናው ተጨማሪ ዕውቀት እንዲሁም ግብዓት ያስገኛል ነው ያሉት። ዶክተር ደሴ በተጨባጭ የክትትል እና ቁጥጥር ሥራ ሲከናወን የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችል ሥልጠና ነው ብለዋል። በተለይ ከበጀት ዝግጅት እና አሥተዳደር አንጻር ጠቃሚ እንደኾነ እና የክትትል እና ቁጥጥር ሥራዎችን ለመከዎን የሚያስችሉ ግብዓቶች እያገኙበት እንደኾነም አስገንዝበዋል። የክልሉ ገንዘብ ቢሮ ኀላፊ ጥላሁን መሐሪ (ዶ.ር) የሥልጠናው ዓላማ የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴ አባላት የመንግሥትን የፋይናንስ አሥተዳደር እና ግዥ ሥርዓቱን ተገንዝበው የሚከታተሏቸውን ተቋማት እንዲደግፏቸው የሚያስችል ነው ብለዋል። የክልሉ ምክር ቤት ተቋማትን የሚከታተልበት አዲስ ደንብ አዘጋጅቷል ያሉት ዶክተር ጥላሁን መሐሪ የበጀት አጠቃቀም፣ የኦዲት እና የፕሮጀክት አፈጻጸሞችንም ይገመግማል ነው ያሉት። በመኾኑም በእነዚህ እና በተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ በቂ ግንዛቤ ለማስጨበጥም የሚያስችል ሥልጠና ስለመኾኑ ተገልጿል። የአማራ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋንቱ ተስፋዬ በመድረኩ ተገኝተው እንዳሉት አሠራርን መሠረት አድርጎ በዕውቀት ላይ የተመሠረተ ቁጥጥር ለማድረግ እና ኀላፊነትን በአግባቡ ለመወጣት የሚያስችል ሥልጠና ነው። ተቋማት የሚመደብላቸውን ውስን ሃብት እውን ለታለመለት ዓላማ እያዋሉት እንደኾነ በዕውቀት ላይ የተመረኮዘ ቁጥጥር ለማድረግ ይረዳል ነው ያሉት አፈ ጉባኤዋ።