# በሶስት ክልሎች ተግባራዊ የሚሆን የ33 ሚሊዮን ዶላር ፕሮግራም ትውውቅ ይፋ ሆነ
የአብከመ ገንዘብ ቢሮ ከዩኒሴፍ ጋር በመተባበር በማስተር ካርድ ፋውንዴሽን በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ በ3 ክልሎች የሚተገበር እና ለ3 ዓመት የሚቆይ የ33 ሚሊዮን ዶላር ፕሮግራም ትውውቅ አድርጓል፡፡ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ገንዘብ ቢሮ ኃላፊ የተከበሩ ጥላሁን መሃሪ(ዶ/ር) በፕሮግራሙ ትውውቅ ላይ ንግግር ባደረጉበት ወቅት ወደ ኢትዮጵያ ብሎም ወደ አማራ ክልል የክልላችን ወጣቶች ቀጥታ ተጠቃሚ የሚያደርግ “ብቁ ወጣት የሚል ፕሮግራም” ቀርፃችሁ ከክልሉ መንግስት ጋር በጋራ ለመስራት ስለመጣችሁ እናመሰግናለን ብለዋል፡፡ ዶ/ር ጥላሁን መሃሪ አያይዘውም ዩኒሴፍ ከአሁን በፊት በጤና፣ በትምህርት፣ በስርዓተ ምግብ፣ በህፃናት እንክብካቤ እና በመሳሰሉት ከክልሉ መንግስት ጋር ለረጅም ጊዜ አብሮ የሰራ መሆኑን በመግለጽ በክልሉ ስም በታላቅ አክብሮት አመስግነው፤ ይህ ፕሮግራም በአግባቡ እንዲተገበር የክልሉ መንግስት በሙሉ አቅሙ እንደሚሰራ በማሳዎቅ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ለፕሮግራሙ መሳካት አስፈላጊውን ትብብርና ጥረት እንዲያደርጉ ሲሉ ቢሮ ኃላፊው ጨምረው አሳስበዋል፡፡ ብቁ ወጣት ፕሮግራም በአገር ደረጃ በአማራ፣ በትግራይና እና በአፋር ክልሎች በተመረጡ 50 ወረዳዎች ተግባራዊ ይደረጋል ያሉት በዩኒሴፍ የኢትዮጵያ ምክትል ኃላፊ ሚስ ማሪኮ ካጐሽማ በማስተር ካርድ ፋውንዴሽን በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ 120,000 የሚሆኑ ወጣቶችን በስራ እድል ፈጠራ፣ በስነልቦና ድጋፍ፣ በትምህርት በአጠቃላይ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ ተጠቃሚ ለማድረግ የሚሰራ ፕሮግራም እንደሆነ ገልፀው እንደ አማራ ክልል ፕሮግራሙ በ23 ወረዳዎች ተግባራዊ እንደሚደረግም በዩኒሴፍ የኢትዮጵያ ምክትል ኃላፊዋ ማሪኮ ካጎሽማ ጨምረው ገልፀዋል፡፡ ይህ ብቁ ወጣት ፕሮግራም ወጣቶችን በማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ ተጠቃሚ የሚያደርግ ሲሆን በአብዛኛው 80% ሴቶችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ በፕሮግራም ትውውቁ ተገልጿል፡፡