በአማራ ክልል የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የተመደበው በጀት ለታለመለት አላማ እንዲውል ቁጥጥር እየተደረገ ነው
በአማራ ክልል የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተመደበው በጀት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል የተጠናከረ ክትትል፣ ቁጥጥርና ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ገንዘብ ቢሮ አስታወቀ፡፡ ቢሮው የ2017 ዓ.ም የስድስት ወራት እቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በደሴ ከተማ እያካሄደ ነው፡፡ በመድረኩ የቢሮው ኃላፊ ጥላሁን መሃሪ(ዶ/ር) እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ከ150 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት በምክር ቤቱ በማጸደቅ ወደ ሥራ ተገብቷል፡፡ የተመደበው በጀት ለታለመለት ዓላማ ጥቅም ላይ እንዲውል የተጠናከረ ክትትል፣ ቁጥጥርና ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በክትትልና ቁጥጥሩም ባለፉት ዓመታት በበጀት አጠቃቀም ዙሪያ ይሰተዋሉ የነበሩ ችግሮች መሻሻላቸውን ተናግረዋል፡፡ ከተመደበው በጀት እስካሁን ከ32 ቢሊዮን ብር በላይ ጥቅም ላይ መዋሉን የተናገሩት የቢሮ ኃላፊው በክልሉ 79 በመቶ ውዝፍ የኦዲት ግኝትም እንዲመለስ መደረጉን ገልጸዋል፡፡ በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራር አባላትን ጨምሮ ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡